ጥር 27, 2026

ቢሾፍቱ ጥር 14 ቀን 2018 ዓ.ም (ከመልሚ) ‎ኢትዮጵያ የከተሞችን የትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለማፋጠን የሚያስችል ታሪካዊ የከተሞች የሀብት ማሰባሰቢያ መርሃ-ግብር ይፋ አደረገች

‎ብልጽግናዋ የተረጋገጠ ኢትዮጵያን  የመገንባት  ራዕይ እውን ለማድረግ፣ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ የከተሞች ፕሮግራም መርሃ-ግብር የመግባቢያ ስምምነት ቢግ ዊን ፊላንትሮፒ (Big Win Philanthropy) ከተባለ አለም አቀፍ ተቋም ጋር (MoU) በይፋ ተፈራርሟል።

‎ከዚህም ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ የከተሞች የሀብት ማሰባሰቢያ መርሃ-ግብር (Ethiopia Cities Resourcing Track) ይፋ ሆኗል።

‎በዝግጅቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ፣ በአፍሪካ ፈጣን ከሚባሉት አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ የከተሞች መስፋፋት እንደ አንድ የኢኮኖሚ ምርታማነት እና የሥራ ዕድል ፈጠራ ምንጭ ተደርጎ መታየት እንዳለበት ገልጸዋል።

‎ሚኒስትሯ ከተሞቻችን ለእነዚህ ተግዳሮቶች የሚሰጡት ምላሽ ውጤታማነት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን የኑሮ ጥራት እና የኢኮኖሚያችንን የረጅም ጊዜ ተወዳዳሪነት ይወስናል ብለዋል።

‎የከተማ ሀብት ማሰባሰብ (Urban Resourcing): ከተሞች መሰረተ ልማቶችን እና መሰረታዊ አገልግሎቶችን በራሳቸው የውስጥ ገቢ በነፃነት በገንዘብ እንዲደግፉ ማስቻል መሆኑን አስታውቀዋል።

‎የሀገር አቀፍ የንብረት ታክስ ማሻሻያ  ዘመናዊ የንብረት ታክስ ሥርዓትን የአካባቢ ገቢ ማመንጫ መሠረት አድርጎ መዘርጋቱን ተናግረዋል።

‎እንደ አዲስ አበባ ያሉ ስኬታማ ከተሞችን አርአያነት በመከተል፣ በመላው አፍሪካ አህጉር የተሳካ የከተማ ትራንስፎርሜሽንን የሚያሳዩ ተጨማሪ አርአያ ከተሞችን ለመፍጠር አልመናል  ሲሉ ክብርት ሚኒስትር ገልጸዋል።

Posted in: ዜና