(የካቲት 09/2017 ዓ.ም ) የዲላ ከተማ መንግሥት ኮሙኒኬሽን

በጌዴኦ ዞን የተጀመሩ የመሠረተ ልማት ስራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ የኢፌዴሪ ከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታ አቶ የትምጌታ አስራት ገልጸዋል ።

በሚኒስትር ደኤታው አቶ የትምጌታ አስራት የተመራው የሱፐርቪዥን ቡድን በዞኑ በተለያዩ የመሰረተ ልማት ስራዎች ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል ።

የሱፐርቪዥን ቡድኑን የሚመሩት አቶ የትምጌታ አስራት ሚንስቴር መስሪያቤቱ በሀገር ዓቀፍ ደረጃ በሚገኙ ከተሞች ቡድኑ በማዋቀር የድጋፍና ክትትል ስራ በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል ።

እንደ ሀገር በከተሞች ሪፎርም ተደርጐ ከፍተኛ ለውጥ እየተመዘገበ እንደሚገኝ የገለጹት ሚንስትር ደኤታው አቶ የትምጌታ ይህንን አጠናክሮ በማስቀጠል በዞን የሚገኙ ከተሞችን ከዚህም በላይ ለማልማት በቅንጅት መስራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል ።

በዞኑ የተጀመሩ የመሠረተ ልማት ስራዎች ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቁ ለማድረግ ሚኒስትር መስሪያቤቱ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አቶ የትምጌታ አረጋግጠዋል ።

የጌዴኦ ዞን ም/አስተዳደርና የግብርና መምሪያ ኃላፊ ታጠቅ ዶሪ (ዶ/ር) የኢፌዴሪ ከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በዞኑ የሱፐርቪዥን ስራ ለማከናወን በመምጣታቸው አመስግነዋል ።

በሚኒስቴር መስሪያቤት አማካኝነት የሚከናወኑ የተለያዩ የልማት ስራዎች በተለይም የቡሌ ሀሮ ዋጩ መንገድ ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቅ ሚኒስቴር መስሪያቤቱ ትኩረት እንዲሰጥ ሀላፊው ጠይቀዋል ።

የዲላ ከተማ ከንቲባ አቶ ዳንኤል ሽፈራው በበኩላቸው የዲላ ከተማ በራሱ አቅም እና በማህበረሰብ ተሳትፎ ከጊዜ ወደ ጊዜ በመሰረተ ልማት ስራዎች የተሻለ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል ።

አቶ ዳንኤል አክለውም ከተማ አስተዳደሩ በኮርደር ልማት እና በሌሎችም ፕሮጀክቶች እያደረገ ያለውን ጥረት የፌዴራል መንግስት እገዛ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል ።

የመድረኩ ተሳታፊዎች በዞኑ በመንገድ ግንባታ ፣ በውሃ ዝርጋታ ፣ በድልድይ ስራ ፣ በኮርደር ልማት ፣ በካሳ ክፍያ እና በሌሎች ፕሮጀክቶች የሚታዩ ክፍተቶችን ለሚኒስትር መስሪያቤት ጥያቄ አቅርበው ማብራሪያ ተሰጥቷል ።

በመጨረሻም በዳላ ከተማ የተሠሩ የልማት ስራዎች ተጎብኝተዋል።የዲላ ከተማ የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን።

Posted in: News