ሚያዝያ 22, 2026
ሚያዝያ 9/2018ዓ.ም
በሀገር አቀፍ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀው የኢትዮጵያ የመሠረተ-ልማትና ኮንስትራክሽን ሣምንት መርሃ ግብር አዲስ አበባ በሚገኘው አዲስ አለማቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በታላቅ ድምቀት ተጀምሯል።
የኢፌዴሪ ም/ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ተመሥገን ጥሩነህ ፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣኖች ፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ተሳታፊዎች የታደሙበት ሀገር አቀፉ ኹነት በደማቅ ስነሥርአት ተጀምሯል።
ኢትዮጵያ ትገነባለች በሚል መሪ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተዘጋጀውና ከሚያዝያ 9 -12/2018ዓ.በሚዘልቀው ኹነቱ ላይ የዘርፉ ተዋናዮችና ባለድርሻ አካላት ኢትዮጵያን ለመገንባት ፣ ዘርፉን በፈጠራ፣ በፍጥነት እና በጥራት ለማላቅ የተደመረ ሃሳብ የሚያፈልቁበት፣ ተሞክሮ የሚለዋወጡበት፣ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት የጋራ ራዕይ የሚሰንቁበት እንዲሁም ዘርፉን ለማላቅ የሚረዱ ብርሃናማ አቅጣጫዎች የሚፈነጥቁበት እንደሚሆን ይጠበቃል።
በዛሬው መርሃግብር ከመሠረተ-ልማት አና ኮንስትራክሽን ዘርፍ አንጻር የተመዘገቡ ሀገራዊ ስኬቶችን፣ የቴክኖሎጂ አማራጮችን አስመልክቶ ልዩ ልዩ ተቋማት የታደሙበት አውደ-ርዕይ በዕለቱ የክብር እንግዳ የተከፈተ ሲሆን ከከፍተኛ የመንግስት አካላት ጋር በመሆን ጉብኝት ተካሂዷል።
በዛሬው ዕለት በታላቅ ድምቀት የተከፈተው እና የከተማና መሠረ-ተ ልማት ሚኒስቴር ከተባባሪ አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ኹነቱ ከሀገራዊ ዘርፉ ስኬቶችና ቀጣይ ብርሃናማ አቅጣጫዎች የተቀዱ ልዩ ልዩ ሰነዶች የሚቀርቡበት የፓናል ውይይት መርሃ ግብሮች ይኖሩታል።